የጉምሩክ ኮሚሽን ያከናወናቸው የለውጥ ተግባራት ለሌሎች ሴክተር መ/ቤቶች ምሳሌ የሚሆኑ ናቸው ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ (የገቢዎች ሚኒስትር)
የገቢዎች ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ እና ሌሎች የተቋሙ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች የጉምሩክ ኮሚሽን ያከናወናቸውን የለውጥ ስራዎች በዛሬው ዕለት በዋነው መ/ቤት ተገኝተው ጎብኝተዋል፡፡
በጉብኝቱ ንግግር ያደረጉት የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ የጉምሩክ ኮሚሽን የሰራቸው ሁለንተናዊ የለውጥ ተግባራት ለሌሎች ሴክተር መ/ቤቶች ምሳሌ የሚሆኑና ሀገራችን የያዘችውን የብልፅግና ጉዞ እውን ለማድረግ የሚረዱ ናቸው ብለዋል፡፡ ምቹ የስራ አካባቢን ከመፍጠር አኳያም ኮሚሽኑ የሰራቸው የለውጥ ስራዎች አመራርና ሰራተኛው በስራ ቦታው ምቾት እንዲሰማውና የላቀ ውጤት ለማምጣት እንዲነሳሳ የሚያስችሉ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
ሚኒስትሯ አክለውም ኮሚሽኑ የአገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን ተግባራዊ ያደረጋቸው የወረቀት አልባ አገልግሎቶች ደንበኞች ባሉበት ቦታ ሆነው የሚፈልጉትን አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ እና በአለማቀፍ ደረጃም ተወዳደሪ የሚያደርጉ ስራዎች ናቸው ብለዋል፡፡ በኮሚሽኑ የተደረጉ የለውጥ ስራዎች በገቢዎች ሚኒስቴርም እንዲተገበሩ ሚኒስትሯ አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡
የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ በበኩላቸው በጉምሩክ ኮሚሽን የተከናወኑ ሁለንተናዊ የለውጥ ስራዎች ጠንክረን በጋራ ከሰራን ሀገራችን በምትፈልገው በሁሉም ዘርፍ የላቀ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ማሳያዎች ናቸው ብለዋል፡፡ ኮሚሽኑ ከዚህ የበለጠ ውጤት ለማምጣትም የትኩረት አቅጣጫዎችን ለይቶ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነም ኮሚሽነር ደበሌ ገልፀዋል፡፡
ኮሚሽነር ደበሌ አክለውም ኮሚሽኑ የያዝነውን የ2015 በጀት ዓመት “የልህቀት ዓመት” ብሎ በመሰየም እንደተቋም በሁሉም ዘርፍ ልህቀትን ለማረጋገጥ እየተሰራ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡