ደረሰኝ አሳትሞ ለመጠቀም የሚሰጥ ፈቃድ

ደረሰኝ በዕቃ ወይም በአገልግሎት ግብይት ላይ ተመሥርቶ ከሻጩ/ አቅራቢው ለገዥው የሚሰጥና ግብይት ስለመፈፀሙ፣ ገንዘብ ስለመሰብሰቡ፣ ዋጋው ስለመከፈሉ ወይም ለወደፊት ለመክፈል ውል መግባቱን የሚያሳይ ሰነድ ነው፡፡

በፌደራል የታክስ አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 983/2008 አንቀጽ 19(4) ታክስ ከፋዮች ደረሰኝ አሳትመው ስለሚጠቀሙበት ሁኔታ፣ የህትመት ድርጅቶችም ደረሰኝ ሲያትሙ ሊያደርጉት ስለሚገባው ጥንቃቄ፣ የደረሰኝ አይነቶች እና ጥቅም ላይ የሚውሉበት ሁኔታ ተደንግጓል፡፡ አዋጁን ለማስፈፀም የታክስ ደረሰኝ አጠቃቀም እና አስተዳደር መመሪያ ቁጥር 149/2011 ወጥቶ በስራ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ መሠረት፡-

ደረሰኝ ለመጠቀም 

=>ከመታተሙ በፊት የተፈቀደና የተመዘገበ  እንዲሁም የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት በተሰጠው ማተሚያ ቤት የታተመ፣

=>በታክስ ባለስልጣኑ ዕውቅና ከተሰጠው ማተሚያ ቤት ወይም በገንዘብ ሚኒስቴር የታተመ

=>በታክስ ባለስልጣኑ ወይም በገንዘብ ሚኒስቴር እንዲታተምና ጥቅም ላይ እንዲውል የተፈቀደ መሆን ይኖርበታል፡፡

   ማንዋል ደረሰኝ ህትመት ፈቃድ አሰጣጥ እና አጠቃቀም 

               1.ግለሰብ ታክስ ከፋይ

የተጨማሪ እሴት ታክስ ተመዝጋቢ ከአንድ በላይ በሆኑ ክልሎች ወይም ከተማ አስተዳደሮች የሚነግድ ወይም ቤት የሚያከራይ ዋና ምዝገባ ባከናወነበት ቦታ ደረሰኝ አስፈቅዶ ማሳተም፣

በእያንዳንዱ ክልል ወይም ከተማ አስተዳደር ለሚያከናውነው ግብይት (ሽያጭ) ይህንን ደረሰኝ እንዲሰጥ፣

  የታተመውን ደረሰኝ ተከፋፍሎ ሲሰራጭ የደረሰኙን ጥራዝ ዝርዝር የደረሰኝ ህትመት ፈቃድ ለሰጠው የታክስ ባለስልጣን በጽሑፍ ማሳወቅ፣

    የህትመት ፈቃድ የሰጠው የታክስ ባለስልጣንም ለታክስ ከፋዩ የፈቀደውን የደረሰኝ አይነትና ብዛትና ስርጭቱን ለሚሰራበት ክልል/ከተማ መረጃ መላክ፣

                2.ድርጅት

በስሩ ቅርንጫፎች ያሉት የንግድ ድርጅት ለቅርንጫፎቹ የሚጠቀምበት የታክስ ደረሰኝ ዋና ምዝገባ ባደረገበት ያሳተመውን ይሆናል፣

ከአንድ በላይ የንግድ ሥራ ዘርፍ እና የንግድ አድራሻ ያለው ታክስ ከፋይ አሳትሞ በሚጠቀምበት ደረሰኝ ላይ ሁሉም ዘርፎች እና አድራሻቸው ተጠቃሎ መታተም ይኖርበታል፤

በተለያየ ቦታ የቅ/ጽ/ቤቶቹ የሚጠቀሙት ተፈቅዶ የታተመውን  ደረሰኝ  መሆኑን፣ የታተመውን ደረሰኝ ተከፋፍሎ ሲሰራጭ የደረሰኙን ጥራዝ ዝርዝር የደረሰኝ ህትመት ፈቃድ ለሰጠው የታክስ ባለስልጣን በጽሑፍ ማሳወቅ አለበት፡፡

የኤሌክትሮኒክስ ደረሰኝ የአጠቃቀም ፈቃድ አሰጣጥ

በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ መጠቀም የማይችል ታክስ ከፋይ የታክስ ባለስልጣኑን በማስፈቀድ የኤሌክትሮኒክስ ደረሰኝ ለመጠቀም፤ በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ መጠቀም የማይችልበትን አሳማኝ ምክንያት ገልጾ ጥያቄውን ታክስ ለሚከፍልበት የታክስ ባለስልጣን በጽሑፍ ማቅረብ አለበት፡፡

ታክስ ከፋዩ በኤሌክትሮኒክስ ደረሰኝ ለመጠቀም ፈቃድ የሚሰጠው፡-

የሚያቀርበው ሶፍትዌር በኮምፒውተር ፕሮግራም አማካኝነት የሚታተመው ደረሰኝ ቢያንስ “ታክስ ደረሰኝ አጠቃቀም እና አስተዳደር መመሪያ ቁጥር 149/2011” ጋር በተያያዘው ደረሰኝ ናሙና ላይ የተመለከቱትን መረጃዎች የሚይዝ ሆኖ ሲገኝ፣ እና

ለታክስ መረጃ ጥቅም ላይ የሚውል መረጃ እንደማይቀየር ለማረጋገጥ እና ተከታታይ የሆነ የደረሰኝ ቁጥር ለማተም በሚያስችል አኳኋን የተዘጋጀ የኮምፒውተር ፕሮግራም መሆኑ ሲረጋገጥ፤

የቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት ሲያገኝ የታክስ ባለስልጣኑ ታክስ ከፋዩን የኮምፒውተር ፕሮግራም ሶፍትዌሩን የሰራውን ሰው ስም፣ የታክስ ከፋይ መለያ ቁጥር እና ህጋዊ የንግድ ስራ ፈቃድ እንዲያቀርብ በማድረግ ጥያቄው በቀረበ በ10 ቀናት ውስጥ ውሳኔውን በጽሑፍ መግለጽ ይኖርበታል፡፡

ጥቅም ላይ የማይውል ደረሰኝ ስለመሰረዝ

ታክስ ከፋዩ የንግድ ሥራውን ሲያቋርጥ ወይም የዘርፍ፣ የአድራሻ እና የስም ለውጥ ሲያደርግ ታትመው ጥቅም ላይ ያልዋሉ ደረሰኞችን እንዲሰረዝ ማድረግ፤

የታክስ ባለስልጣኑ እንዲሰረዝ በቀረበለት በእያንዳንዱ ደረሰኝ ቅጠል ላይ VOID የሚል ማህተም በማድረግ ለታክስ ከፋዩ መመለስ፤

   VOID የተደረገውን ደረሰኝ ብዛት እና ሴሪያል ቁጥር የሚገልጽ ማረጋገጫ ለታክስ ከፋዩ መስጠት፤

   ታክስ ከፋዩ ዘርፍ የቀነሰ እንደሆነ በእጁ ላይ ያለው ደረሰኝ ሳይሰረዝ የንግድ ስራውን ለቀጠለበት ዘርፍ ጥቅም ላይ እንዲውል በታክስ ባለስልጣኑ ሊፈቀድ ይችላል፡፡

   ታክስ ከፋዩ ተጠያቂነት

ያሳተመውን ደረሰኝ በትውስት ወይም በሽያጭ ወይም በማንኛውም መልክ ለሶስተኛ ወገን እንዲጠቀምበት አሳልፎ የሰጠ እንደሆነ፣

ግብይት ሳይኖር ግብይት እንደተፈፀመ በማስመሰል ለሶስተኛ ወገን የሰጠ እንደሆነ፣

ግብይት ፈጽሞ ደረሰኝ ያልሰጠ እንደሆነ ፣

በደረሰኙ በራሪና ቀሪ ላይ የተለያየ የገንዘብ መጠን አስፍሮ የተገኘ እንደሆነ፣ እና ሌሎች ተግባራት

የማተሚያ ቤት ኃላፊነት

  ማንኛውም ታክስ ከፋይ ደረሰኝ ለማሳተም ወደ ማተሚያ ቤቱ ሲመጣ፡-

ታክስ ከፋዩ ደረሰኝ እንዲያሳትም ከታክስ ባለስልጣኑ ደብዳቤ የተጻፈለት መሆኑን፣ 

የህትመት ጥያቄውን ያቀረበው ሰው ታክስ ከፋዩ ራሱ ወይም ወኪሉ መሆኑን የማረጋገጥ፣

የህትመት አገልግሎት የተሰጣቸውን ታክስ ከፋዮች ዝርዝር የያዘ ሪፖርት በየሩብ ዓመቱ ታክስ ለሚከፍልበት ቅ/ጽ/ቤት የማቅረብ፣

የህትመት አገልግሎት የሚሰጥበትን አድራሻ ሲቀይር ታክስ ለሚከፍልበት ቅ/ጽ/ቤት የማስታወቅ ግዴታ፣ሌሎች ከህትመቱ ጋር ተያያዝ የሆኑ ተግባራት በጥንቃቄ እንዲፈጸም ኃላፊነት ሆኖ መካተቱ

የታክስ ባለስልጣኑን ፈቃድ ሳያስፈልግ ሊታተሙ የሚችሉ ሰነዶች

ታክስ ከፋዩ ደረሰኝ ያልሆኑ ሌሎች ከንግድ ስራ ጋር የተያያዙ የሚከተሉት ሰነዶች የታክስ ባለስልጣኑን ፈቃድ መጠየቅ ሳያስፈልገው የሚያሳትማቸው፣

1/ የዕቃ ማስተላለፊያ ሰነድ /Delivery Order/፣

2/ የዋጋ ማቅረቢያ ኢንቮይስ /Proforma invoice/፣

3/ የዋጋ መጠየቂያ ቢል (Payment request Bill)፣

4/ ድርጅቶች ለውስጥ ቁጥጥር የሚጠቀሙባቸው እንደ የገንዘብ ወጪ ማዘዣ ደረሰኝ (payment voucher) እና

5/ ሌሎች ተመሳሳይ የህትመት ሰነዶች፣

  •  

.

በብዛት የተነበቡ ዜናዎች

  • "ከፍተኛ ግብር ከፋዮች የታክስ ህግን በማክበርና የልዕቀት ማዕከል በመሆን አርአያ ሊሆኑ ይገባል" የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው Fri, 29 Oct 2021
"ከፍተኛ ግብር ከፋዮች የታክስ ህግን በማክበርና የልዕቀት ማዕከል በመሆን አርአያ ሊሆኑ ይገባል" የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው
  • "የሀገራችንን ኢኮኖሚ በጽኑ መሰረት ላይ ለማቆም በሚደረገው ጥረት የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን ያላቸው ድርሻ ከፍተኛ በመሆኑ ለአፍታም ቢሆን ሳናሸልብ ተግተን እንሰራለን " ወ/ሮ አይናለም ንጉሴ (የገቢዎች ሚኒስትር) Wed, 4 Jan 2023
"የሀገራችንን ኢኮኖሚ በጽኑ መሰረት ላይ ለማቆም በሚደረገው ጥረት የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን ያላቸው ድርሻ ከፍተኛ በመሆኑ ለአፍታም ቢሆን ሳናሸልብ ተግተን እንሰራለን " ወ/ሮ አይናለም ንጉሴ (የገቢዎች ሚኒስትር)