የጉምሩክ ኮሚሽን የካርጎ ትራኪንግ አገልግሎት ለማሻሻል ስምምነት ተፈራረመ
የጉምሩክ ኮሚሽን የካርጎ ትራኪንግ አገልግሎትን ዘመኑ በደረሰበት ቴክኖሎጂ ለመደገፍ ከትሬድ ማርክ ኢስት አፍሪካ ካምፓኒ ጋር በዛሬው ዕለተው የስራ ስምምነት ተፈራርመዋል፡፡
ስምምነቱን የጉምሩክ ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ እና የትሬድ ማርክ ኢስት አፍሪካ ካምፓኒ ተወካይ አቶ ታደሰ ይማሙ ተፈራርመዋል፡፡
በስምምነት መርሀ ግብሩ ላይ የጉምሩክ ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ እንደተናገሩት ኮሚሽኑ በአዲስ መልክ ከተቋቋመበት ወቅት አንስቶ የጉምሩክ አገልግሎቱን ምቹ፣ ዘመናዊና ቀልጣፋ ለማድረግ ጥረቶችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የራሱን አቅም ከማሳደግ ጎን ለጎን ከተለያዩ አለም አቀፍ የልማት አጋሮች ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ከትሬድ ማርክ ኢስት አፍሪካ ካምፓኒ ጋር የሚኖረን የስራ ስምምነትም ይሄንኑ ያሳያል ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፡፡ በተለይም በድንበሮች አካባቢ ያለውን የገቢና ወጪ ዕቃዎችን ፍሰት ጤናማ፣ ቀልጣፋና ግልፅ ለማድረግ የካርጎ ትራኪንግ ቴክኖሎጂ ወሳኝ በመሆኑ ከካምፓኒው ጋር በዚህ ረገድ በትብብር ለመስራት ዝግጅት መጠናቀቁንም ጠቁመዋል፡፡
ቴክኖሎጂው በጉምሩክ ክልል ውስጥ የሚጓጓዙ ዕቃዎች ያሉበትን ሁኔታ፣ የደረሱበትን ቦታና አሁናዊ መረጃ በግልፅ ከማሳየቱም በላይ በህጋዊ ዕቃዎች ውስጥ የሚገቡ ህገወጥ ዕቃዎችን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡ በዚህ ረገድ ካምፓኒው በሙሉ አቅሙ ስራውን እንደሚደግፍ እንተማመናለን ያሉት ኮሚሽነሩ ጉምሩክ ኮሚሽንም ስራው ውጤታማ ሆኖ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል፡፡
የትሬድ ማርክ ኢስት አፍሪካ ካምፓኒ ተወካይ የሆኑት አቶ ታደሰ ይማሙ በበኩላቸው ድርጅታቸው በተለይም በምስራቅ አፍሪካ የጉምሩክ አገልግሎትን ለማቀላጠፍ በሚሰሩ ስራዎች በመሳተፍ ከፍተኛ ልምድ ያለው ነው ብለዋል፡፡ ከካርጎ ትራኪንግ ቴክኖሎጂ ጋር በተያያዘም ከኮሚሽኑ ጋር በቅርበት በመነጋገር ወደ ስራ በመግባት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በ 18 ወራት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ የገለፁት የካምፓኒው ተወካይ ጥናቶች ተደርገው የማሽን ተከላ ከማድረግ ባሻገር ለሰራተኞች የተለያዩ ስልጠናዎች እንደሚሰጡ በዚሁ ወቅት ገልፀዋል፡፡