በበጀት ዓመቱ ከ336 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
የገቢዎች ሚኒስቴር ባሳለፍነው በ2014 በጀት ዓመት ከ336 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው አስታወቁ፡፡
ሀገራችን በ2022 ሀገራዊ የታክስ አስተዳደር ተገንብቶ ሀገራዊ ወጪን በራሷ ገቢ ለመሸፈን የምታደርውን ጥረት ለማሳካት ተልእኮ የተሰጠው የገቢዎች ሚኒስቴር በስኬት ገቢን የመሰብሰብ አቅሙ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
ለዚህም ማሳያ የሚሆነው ሚኒስቴሩ በዚህ በጀት ዓመት ሊሰበስብ ካቀደው 360ቢሊዮን ብር ውስጥ 336ቢሊዮን 710ሚሊየን 021ሺ 930ብር በመሰብሰብ የእቅዱን 93.53 በመቶ ማሳካቱ ነው፡፡
አፈጻፀሙ ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻፀር የብር 57ቢሊዮን 494ሚሊየን 923ሺ 697 ወይም የ20.59 በመቶ እድገት እንዳለው ሚኒስትሩ አቶ ላቀ አያሌው ተናግረዋል፡፡
የተሰበሰበው ገቢ ምንጭ ከአገር ውስጥ ታክስ 196ቢሊዮን 211ሚሊየን 638ሺ 548ብር የሚሸፍን ሲሆን ከውጭ ንግድ ቀረጥና ታክስ ደግሞ 140ቢሊዮን 498ሚሊየን 338ሺ 382ብር መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል፡፡
ገቢው በአገራችን በተፈጠረው ጦርነት ብዙ ተቋሞቻችን ከስራ ውጭ በሆኑበት፣ በጦርነቱ ምክንያት የንግዱ እንቅስቃሴ በተቀዛቀዘበት፣ በተለያዩ አካባቢዋች በሚፈጠሩ ግጭቶች ተቋሞቻችን በአግባቡ ስራቸውን እንዳይሰሩ በተቸገሩበት እንዲሁም የንግዱ ማህበረሰብ ስራውን ተረጋግቶ ባልሰራበት ሁኔታ ውስጥ በመሰብሰቡ የተሻለ አፈጻጸም ሊያስብለው እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡
የህገ-ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ እንዲሁም የሀሰተኛ ግብይት ለገቢ አሰባሰቡ ትልቅ ተግዳሮት ቢሆንም ይህንን ለመሻገር የገቢዎች ሚኒስቴር ከህብረተሰቡ እና ከባለድርሻ አካላት ጋር የሚሰራቸው ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው የቀጠሉ ቢሆንም ሕገ-ወጥ ድርጊቱ ሙሉ በሙሉ ባልተቀረፈበት ሁኔታ ገቢያችን በዚህ ደረጃ መሰብሰቡ የተቋሙን ስኬታማነት ማሳያ ነው ሲሉ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡
በ2022 ሀገራዊ የታክስ አስተዳደር ተገንብቶ ሀገራዊ ወጪን በራሷ ገቢ ለመሸፍን የሚደረገውን ጉዞ ለማሳካት በምናደርገው ጉዞ በ2010 በጀት ዓመት 152ቢሊየን ብር፣ በ2011 በጀት ዓመት 198ቢሊዮን፣ በ2012 በጀት ዓመት 233 ቢሊየን፣ በ2013 በጀት ዓመት 279 ቢሊዮን ብር እንዲሁም በ2014 በጀት ዓመት 336 ቢሊየን ብር መሰብሰብ መቻላችን የገቢውን እድገት ቀጣይነት ጠቋሚ ነው፡፡
ሚኒስትሩ፤ የገቢ አፈጻጸሙ የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን አመራሮችና ሰራተኞች በኃላፊነት መንፈስ የገቢ ምንጮችን ሁሉ በመዳሰስ እና ከልብ መስራት በመቻላቸው፣ ግብር ከፋዮቻችን ግብራቸውን አሳውቀው ያለምንም ሰበብ ግብራቸውን በወቅቱ መክፈል በመቻላቸው እንዲሁም አጋር አካላትና ህዝባችን ባደረገው ያልተቋረጠ ድጋፍ የተገኘ ውጤት በመሆኑ በራሴና በገቢዎች ሚኒስቴር ስም ከልብ የመነጨ አክብሮትና ምስጋና በያላችሁበት ይድረሳችሁ ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል::