የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን ለኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸውን ቁሳቁሶች ድጋፍ አደረጉ
የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በሰው ሰራሽ እና የተፈጥሮ አደጋዎች ጉዳት ለደረሰባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ማቋቋሚያ የሚሆን ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው አልባሳትና ምግብ ነክ ቁሳቁሶችን ድጋፍ አድርገዋል ።
ድጋፉን የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ እና የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ በከሚሴ ከተማ ተገኝተው አስረክበዋል።
በድጋፍ ርክክቡ ወቅት ንግግር ያደረጉት የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ አይናለም ንጉሴ፤ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እና የጉምሩክ ኮሚሽን በመንግስት ከተሰጣቸው ተግባርና ኃላፊነት ባሻገር በተለያዩ የሃገሪቱ አካባቢዎች ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ሰብአዊ እርዳታ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።
በተቋማት የሚደረጉ ድጋፎች ችግሮችን በጊዚያዊነት ለማለፍ እንደሚረዱ የጠቀሱት ሚኒስትሯ ዞኑም የሚያጋጥሙትን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በዘላቂነት ለመቅረፍ ያለውን አቅም በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባውም አስገንዝበዋል።
የጉምሩክ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ በበኩላቸው፤ ሃገራችንን በየጊዜው የሚፈትኗትን የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ኮሚሽኑ የበኩሉን አስተዋፅኦ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ለኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን የተደረገው ድጋፍም የዚሁ አንድ አካል መሆኑን አስረድተው ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ አልባሳት እና የፍጆታ እቃዎች ድጋፍ መደረጉን ተናግረዋል ።
ከለውጡ በኋላ ሰብአዊ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ከስምንት ቢሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ ቁሳቁሶችን ኮሚሽኑ ድጋፍ ማድረጉንም ኮሚሽነር ደበሌ ገለጸዋል።
ድጋፉን የተረከቡት የከሚሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወ/ሮ ከድጃ አሊ፣ ድጋፉ በጦርነት እና በሌሎች ተፈጥሮአዊ አደጋዎች ጉዳት ለደረሰባቸው አካላት በትክክል እና በወቅቱ እንደሚያደርሱ አስረድተዋል።
በብዛት የተነበቡ ዜናዎች
-
Fri, 29 Oct 2021"ከፍተኛ ግብር ከፋዮች የታክስ ህግን በማክበርና የልዕቀት ማዕከል በመሆን አርአያ ሊሆኑ ይገባል" የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው
"ከፍተኛ ግብር ከፋዮች የታክስ ህግን በማክበርና የልዕቀት ማዕከል በመሆን አርአያ ሊሆኑ ይገባል" የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው
-
Wed, 4 Jan 2023"የሀገራችንን ኢኮኖሚ በጽኑ መሰረት ላይ ለማቆም በሚደረገው ጥረት የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን ያላቸው ድርሻ ከፍተኛ በመሆኑ ለአፍታም ቢሆን ሳናሸልብ ተግተን እንሰራለን " ወ/ሮ አይናለም ንጉሴ (የገቢዎች ሚኒስትር)