የታቀደው ገቢ እንዲሰበሰብ ተግቶ መሥራት እንደሚገባ ተጠቆመ
ለአንድ ሀገር ኢኮኖሚ ቀጣይነት እና ዘላቂነት አስተማማኙ ከሀገር ውስጥ የሚሰበሰብ ገቢ በመሆኑ አስፈላጊውን ጥረት እና አቅም አሟጦ መጠቀም እንደሚገባ የገቢዎች ሚኒስትር አሳሰቡ፡፡
ሚኒስትሯ ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ የ2015 የመጀመሪያው ሩብ ዓመት አፈጻጸም ሲገመገም እንዳሉት፤ ሀገራችን አሁን ካለችበት አስቸጋሪ ሁኔታ አንጻር ከምንም ጊዜ በላይ ገቢ የሚያስፈልጋት እንደመሆኑ ገቢያችንን በሚፈለገው መጠን ለመሰብሰብ ሁሉም ቅ/ጽ/ቤቶች የሰው ኃይላቸውን በትጋት በማንቀሳቀስ ሥራዎችን በልዩ ትኩረትና ርብርብ መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
በዓመቱ ከፍተኛ ገቢ ከሚሰበሰብባቸው ወራት መካከል ጥቅምት አንዱ በመሆኑ የተያዘውን ከ56.9 ቢሊዮን ብር በላይ የመሰብሰብ ዕቅድ ለማሳካት ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች አቅማቸውን አሟጠው እንዲጠቀሙ፤ የዋናው መሥሪያ ቤት አመራሮች ደግሞ ወደ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ወርደው በቅንጅት ማገዝ እና ችግሮችን ከስር ከስር መቅረፍ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ የቴክኖሎጂ ችግር እንዳያጋጥም መጣር ካጋጠመም በፍጥነት ለመፍታት እንዲቻል ቋሚ የድጋፍ ስልት መዘርጋት እንደሚገባ እና ግብር ከፋዮችን ለመቀስቀስ የኮሙኒኬሽን ስራዎችን በተገቢው መንገድ መሰራት አለባቸው ሲሉም አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡
ግምገማውን አዳማን ጨምሮ አዲስ አበባ ውስጥ የሚገኙ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች በአካል እና የባህርዳር፣ የሀዋሳ፣ የጅማ፣ የኮምቦልቻ እና የድሬዳዋ ግብር ከፋዮች ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጆች ደግሞ በቪዲዮ ኮንፈረንስ በመታገዝ የተካፈሉ ሲሆን የገቢ እቅዱን ለማሳካት ያላቸውን ዝግጁነት ገልጸዋል፡፡
በ2015 የመጀመሪያው ሩብ ዓመት ከሀገር ውስጥ ታክስ እና ከወጪ ንግድና ቀረጥ 95 ቢሊየን 184.36 ሚሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ 93 ቢሊየን 348.46 ሚሊየን ብር ገቢ የተሰበሰበ ሲሆን ክንውኑም 98.07 በመቶ ነው፡፡ ይህ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ23 ቢሊየን 308.49 ሚሊየን ብር ወይም በ33.28 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡
በዚሁ ጊዜ 8 ቢሊዮን 252 ሚሊዮን 995ሺ 989 ብር የውዝፍ እዳ ለመሰብሰብ ታቅዶ 8 ቢሊዮን 858 ሚሊዮን 922ሺ 885 ብር መሰብሰብ ተችሏል፡፡
እስካሁን ለተመዘገበው ውጤት የግብር ሰብሳቢው ተቋም ሰራተኞች፣ ግብር ከፋዮች እና ባለድርሻ አካላት አስተዋጾአቸው ከፍተኛ በመሆኑ ምስጋና ያቀረቡት ሚኒስትሯ በጥቅምት ወር የተያዘውን ከ56.9 ቢሊየን ብር በላይ እቅድ እንዲሁም የቀሪ የበጀት ዓመቱ ዕቅድን ከታቀደው በላይ ለመሳካት መሰራት እንዳለበት እና ግብር ከፋዮች እና ባለድርሻ አካላት ከተቋማችን ጋር በመሆን እንዲረባረቡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ዜና
"ውጤታማነት በጅማ"